fbpx

Leave Your Immigration Worries In Our Hands

  1. Home
  2.  » 
  3. Amharic
  4.  » Applying For Asylum The Process

Applying For Asylum – The Process

የፖለቲካ ጥገኝነት ሒደት ምን ይመስላል?

ጥገኝነት ለውጭ አገር ዜጋዎች የሚሰጥ የጥበቃ ዓይነት ነው። የሚሰጠውም

  • በአሜሪካ ድንበር ክልል ውስጥ ለሚገኙ ወይም
  • ጠረፍ ላይ ሆነው ለመግባት ለሚያመለክቱ ግለሰቦች ሲሆን ግለሰቦቹ

‹‹እ.ኤ.አ. በ1951 ዓ.ም. በወጣው የተባበሩት መንግስታት ስምምነት (ኮንቬንሽን) እንዲሁም እ.ኤ.አ. በ1967 ዓ.ም. በወጡት ፕሮቶኮሎች ውስጥ ‹‹ለስደተኛ የተሰጠውን ትርጓሜ የሚያሟሉ መሆን ይገባቸዋል፡፡ በዚህ ትርጓሜ ስደተኛ ማለት ወደ አገሩ/አገሯ ለመመለስ የማይችል/የማትችል ወይም ፈቃደኛ ያልሆነ/ያልሆነች እና ‹‹በዘር፣ በኃይማኖት፣ በዜግነት፣ በማህበራዊ ቡድን አባልነት ወይም በፖለቲካ አስተሳሰብ ሳቢያ›› ቀደም ሲል በተፈጸመ መሳደድ (persecution) ወይም ወደፊት ሊፈጸም በሚችል መሳደድ ፍርሃት ምክንያት በትውልድ አገሩ/አገሯ ጥበቃ ማግኘት የማይችል/የማትችል ማለት ነው፡፡ የአሜሪካ ሕግ አውጪው አካል (ኮንግረስ) ይህንኑ ትርጓሜ እ.ኤ.አ. በ1980 ዓ.ም. በአሜሪካ የኢሚግሬሽን ሕግ ውስጥ በማካተት ይመራበታል፡፡ የፖለቲካ ጥገኝነት በፖለቲካ በደል ችግር ለደረሰባቸው ብቻ ሳይሆን የተለያዪ ማሕበራዊ፡ ፆታዊ፡ ቤተሰባዊ፡ ሃይማኖታዊ መከራዎችን ያለፉትን ሊያጠቃልል ይችላል። በተጨማሪም አንድ/አንዲት የጥገኝነት አመልካች በአካል አሜሪካ ከገቡበት ጊዜ ጀምሮ በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ የጥገኝነት ማመልከቻቸውን ማስገባት ይኖርባቸዋል፤ ይህንን ካላደረጉ ደግሞ ለዘገዩበት በቂ ምክንያት የሚሆኑ የልዩ ሁኔታ መስፈርቶችን ማሟላት ይገባቸዋል፡፡ አንድ ሰው ለጥገኝነት የሚያመለክትበት ሁለት መንገዶች አሉ፡ በአዎንታዊ እና በመከላከል፡፡

አዎንታዊ ጥገኝነት

  • በአሜሪካን አገር ውስጥ ያሉ አንድ/አንዲት ግለሰብ ከአገር በማስወጣት (deportation) ሂደት ላይ ካልሆኑ ወይም ድንበር ላይ ተይዘው ካልሆነ ግለሰቡ/ግለሰቧ ለጥገኝነት በአዎንታዊ መንገድ ለማመልከት ይችላሉ፡፡ ይህም የሚደረገው ፎርም I-589ን ሞልቶ በማጠናቀቅና ግለሰቡ በሚኖሩበት ግዛት (ስቴት) ወይም ከተማ በላይ ለሆነው የአገልግሎት ማዕከል (service center) የማየት ስልጣን ላለው የአሜሪካ የዜግነት እና የኢሚግሬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት (United States Citizenship and Immigration Office) የአገልግሎት ማዕከል በማስገባት ነው፡፡ ማመልከቻው ተጠናቅቆ ከገባ በኋላ ይሄው የአገልግሎት ማዕከል (service center) ለሚመለከተው ከተማ ጽ/ቤት ልኮ (USCIS) ለአመልካች የባዮሜትሪክ መምሪያዎችን ይሰጣል፡፡ መምሪያዎቹም አሻራ መስጠትን እና ባዮሜትሪኮችን አመልካች ሄደው እንዲያጠናቅቁ ያዛሉ ነው፡፡
  • በአሜሪካ ውስጥ ያሉት የጥገኝነት ጽ/ቤቶች ስምንት ብቻ ሲሆኑ እያንዳንዳቸው የበርካታ ግዛቶችን (ስቴቶችን) እና ከተማዎችን ጉዳዮች የማየት ስልጣን አላቸው፡፡ ለምሳሌ የሳን ፍራንሲስኮ የጥገኝነት ጽ/ቤት የሰሜን ካሊፎርኒያን፣ የሪኖ ኒቫዳን፣ የዋሺንግተንን እና የኦረገንን ጉዳዮች የማየት ስልጣን አለው፡፡
  • አሁን ባለው የጉዳዮች መጓተት የተነሳ ለቃለ መጠይቅ ቀጠሮ ለማግኘት ከሁለት እስከ አምስት ዓመታት ሊፈጅ ይችላል፡፡ የተወሰኑ የጥገኝነት ጽ/ቤቶች ለአጣዳፊ ጉዳዮች እና ለሌሎች አስገዳጅ ምክንያቶች የቀጠሮ ጊዜውን ለማቅረብ ይቻል ይሆናል፡፡

የጥገኝነት ቃለ መጠይቅ ሂደት

  • በቃለ መጠይቁ ጊዜ አመልካቹ/አመልካቿ የሚቀርቡት ከአስተርጓሚ ጋር ወይም እንግሊዝኛ በደንብ የሚናገሩ ከሆነ በራሳቸው እና ጠበቃ ካላቸው ከጠበቃቸው ጋር ነው፡፡
  • የጥገኝነት ቃለ መጠይቁ የሚፈጸመው በቃለ መሃላ ሲሆን በእንደዚህ ዓይነት ጉዳዮች ላይ ለመወሰን ስልጠና በተሰጠው/በተሰጣት የጥገኝነት ባለስልጣን (Asylum Officer) ነው፡፡
  • የቃለ መጠይቁ ሂደት አንድ/አንዲት ግለሰብ ለምን ለጥገኝነት እንደሚያመለክቱ፣ በአገራቸው እያሉ ምን ዓይነት ገጠመኞች እንደነበሯቸው እንዲሁም ቢመለሱ ደግሞ ምን ፍራቻ እንዳለባቸው ለመግለጽ እድል የሚያገኙበት ነው፡፡ የጥገኝነት ባለስልጣኑ/ኗ ኃላፊነት ሁሉንም መረጃዎች እንዲገለጡ ማድረግ እና የሚጣረሱ ነገሮች ወይም ውሸቶች ካሉ አመልካቹን/አመልካቿን መፈተንም ነው፡፡ አስተርጓሚ በጥቅም ላይ ከዋለ የጥገኝነት ጽ/ቤቱ የአመልካችን ቋንቋ የሚናገርና ትርጓሜው ትክክል መሆኑን የሚያረጋግጥ የአስተርጓሚ ተቆጣጣሪ በስልክ ይጠራሉ፡፡
  • የጥገኝነት ጽ/ቤቱ ፎርሙን በመመልከት አመልካች በመሃላ ፈርመው ከማረጋገጣቸው በፊት የሚደረጉ ለውጦች ወይም የሚጨመሩ አዳዲስ ነገሮች እንዳሉ ይጠይቃሉ፡፡
  • ከቃለ መጠይቁ በፊት አመልካች የጽሑፍ ቃለ መሃላ ፎርም ፈርመው በቃላቸውም የምስክርነት ቃላቸው፣ ማስረጃዎቻቸው እና ይዘቶቻቸው በሙሉ ትክክል ስለመሆናቸው ይምላሉ፣ ያረጋግጣሉ፤ እያወቁ ሀሰተኛ መረጃ መስጠት በቅድሚያ ከባድ የገንዘብ ቅጣት እና እስራትን የሚያስከትል ወንጀል ከመሆኑም ሌላ የኢሚግሬሽን ጥቅሞችን የሚያስቀር መሆኑ ግልጽ እንደሆነላቸውም ያሳውቃሉ፡፡ አንድ/አንዲት አመልካች እያወቁ የሀሰት መረጃ ከሰጡ ቅጣቶቹ ከባድ ሲሆኑ የፍትሐ-ብሔር እና የወንጀል ቅጣቶችን እንዲሁም ለማንኛውም የኢሚግሬሽን ጥቅም ማመልከት አለመቻልን ይጨምራሉ፡፡
  • ቃለ መጠይቁ ከአንድ ሰዓት እስከ ከግማሽ ቀን ወይም በርካታ ቀናት ሊፈጅ ይችላል፡፡ ብዙ ጊዜ ግን ቃለ መጠይቁ በአማካይ 2.5 ሰዓታት ገደማ ይወስዳል፡፡
  • የጥገኝነት ባለስልጣኑ/ኗ ከአመልካች የምስክርነት ቃል ይወስዳሉ፣ ሊታመን የሚችል መሆኑን ይገመግማሉ፣ የስደተኛን የሕግ ትርጓሜ መስፈርት ስለመሟላቱ ያያሉ፤ ከዚያ በኋላ በጉዳዩ ላይ ውሳኔ ይሰጣሉ፡፡ አመልካች በቃል ምስክርነታቸው ሊታመኑ የሚችሉ መሆናቸው ምናልባት ከሁሉም በላይ ለጉዳዩ መልካም ውጤት ዋና ነገር ነው፡፡ የሚወስነው ጠቃሚ ነገር ነው፡፡ አመልካቾች ቃላቸውን ሲሰጡ አፍረጥርጠው መናገር ይገባቸዋል፤ እንዲሁም ሁሉንም ጥያቄዎች በዝርዝር እና በእውነት መመለስ አለባቸው፡፡ በተለይም ጠቃሚ የሚሆነው አመልካች ጥያቄው ካልገባቸው ወይም መልሱን ካላወቁት ለጥገኝነት ባለስልጣኑ/ኗ ያንኑ መናገር አለባቸው፡፡ አመልካች ከመገመት፣ ከመቀባባት (ወሬ ለማጣፈጥ እውነት ያልሆኑ ነገሮችን ከመጨመር) ወይም ዝም ብሎ ከመስማማት መቆጠብ አለባቸው፡፡ የጥገኝነት ቃለ መጠይቅ በጽ/ቤት ውስጥ የሚፈጸም ቢሆንም የፍርድ ቤት ድባብ ያለውና ለጥገኝነት ባለስልጣኑ/ኗ ውሳኔ የማስተላለፍ እኩል ስልጣን የተሰጠበት ነው፡፡
  • ቃለ መጠይቁ ሲጠናቀቅ አመልካች ውሳኔያቸውን ለመቀበል በሁለት ሳምንታት ውስጥ ተመልሰው እንዲሄዱ ማስታወሻ ይሰጣቸዋል፡፡ ከዚያ በኋላ የጥገኝነት ባለስልጣኑ/ኗ ማስታወሻቸውን ከነውሳኔ ሃሳባቸው ጽፈው በበላይ ሃላፊ ታይቶ እንዲጸድቅ ያደርጋሉ፡፡ አንዳንድ ጉዳዮችን በሚመለከት ከጉዳዩ ውስብስብነት የተነሳ ወይም ተጨማሪ ምርመራ የሚጠይቅ በመሆኑ በሌሎች የመንግስት አባላት መታየት ሊኖርበት ይችላል፡፡
  • የጥገኝነት ጽ/ቤቱ ከሦስት ውሳኔዎች አንዱን ውሳኔ ሊሰጥ ይችላል፡፡
    • የመጀመሪያው ውሳኔ ጥገኝነት መስጠት ነው፡፡ ይህም ማለት ግለሰቡ/ግለሰቧ የስደተኛን ትርጓሜ መስፈርት አሟልተዋል እንዲሁም ላልተወሰነ ጊዜ የጥገኝነት ጥበቃ ተሰጥቷቸዋል ማለት ነው፡፡
    • ሁለተኛው ውሳኔ ጥገኝነት ያለመስጠት ሃሳብ እንዳለ ማሳወቂያ ነው፡፡ ይህም የሚሰጠው የቪዛ ቆይታው ላልተቃጠለባቸው (lawful nonimmigrant status) አመልካች ብቻ ነው፡፡ ጥገኝነት ያለመስጠት ሃሳብ ማሳወቂያ ሲሰጥ አመልካች በማሳወቂያው ላይ ላሉት ምክንያቶች ምላሽ ለመስጠት አስራ ስድስት ቀናት ይኖራቸዋል፡፡ ይህን ማድረግ ካልቻሉ ግን የጥገኝነት ጽ/ቤቱ ጥገኝነት የመከልከል ውሳኔ ያስተላልፋል፡፡
    • ሦስተኛው ውሳኔ አመልካች የቪዛ ቆይታ ገደቡ የተቃጠለ ወይም ሌላ ሕጋዊ መቆያ የሌለው ሲሆን ነው፡፡ የጥገኝነት ጽ/ቤቱ ጉዳዩን ወደ ኢሚግሬሽን ፍ/ቤት በመምራት ከአገር የማስወጣት (የመጠረዝ) ሂደት ያስጀምራል፡፡ አመልካች የጥገኝነት ማመልከቻቸውን ለኢሚግሬሽን ፍርድ ቤት እንደገና ማቅረብ ይችላሉ፡፡ ጉዳዩም እንደ አዲስ ይታያል፡፡

የመከላከል ጥገኝነት ማመልከቻ

አንድ/አንዲት ግለሰብ ጠረፍ ላይ ወይም አገር ውስጥ የተያዙ ከሆነ ከአሜሪካ ሊጠረዙ መሆን ወይም አለመሆናቸውን ለመወሰን በኢሚግሬሽን እና ጉምሩክ አስፈጻሚ መሠረታዊ ቃለ መጠይቆች ይደረግላቸዋል፡፡ ግለሰቡ/ግለሰቧ ወደ አገሬ ተመልሼ መሄድ እፈራለሁ ካሉ የኢሚግሬሽን እና ጉምሩክ አስፈጻሚ ግለሰቡን/ግለሰቧን ሊታመን የሚችል (እውነታ ያለው) ፍርሃት ስለመኖሩ ቃለ መጠይቅ እንዲደረግላቸው ጉዳዩን ይመሩታል፡፡ ሊታመን የሚችል ፍርሃት እንዳለ ከተረጋገጠ ጉዳዩ ወደ ፍ/ቤት ይመራል፡፡ በዚህ ጊዜ ግለሰቡ/ግለሰቧ በቁጥጥር ስር ያሉ ከሆነ እና 1. ለአገሪቱ ጎጂ ያልሆኑ እና አደጋ ወይም ወንጀል የማያደርሱ ከሆኑ፣ እና 2. ቤተሰባዊ ግንኙነቶች ካሏቸው፣ እና 3. ፍ/ቤት ቀጠሮ የሚከታተሉ ከሆነ ድንበር ጥሰው ከገቡ ብኃላ ከሆነ ፍርድ ቤት በዋስትና የመለቀቅ ምብቶን ይመረምራል። ጠረፍ ላይ እጅ ሰጥተው ከሆነ የኢምግሪሽንና ጉምሩክ ጽ/ቤት ብቻ በገንዘብ ዋስትና ሊፈቱ የሚችሉበት ሁኔታዎች እንዲኖሩ ያስችላል፡፡ እነዚህ ግለሰቦች ናቸው በአሁኑ ጊዜ የመከላከል የጥገኝነት ማመልከቻ በኢሚግሬሽን ፍርድ ቤት ለማቅረብ የሚችሉት፡፡

  • አሁን ‹‹ተጠሪ›› ተብለው የሚጠሩት አመልካቹ/አመልካቿ ጉዳያቸውን የማየት ስልጣን ላለው ፍርድ ቤት ማመልከቻ ያስገባሉ፣ አንድ ቅጂ ለመንግስት ይሰጣሉ፤ ከዚያም የባዩሜትሪክስ መምሪያዎችን የከፊል ቅጂ ለአገልግሎት ማዕከሉ (USCIS) ይልካሉ፡፡ በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ ግለሰቡ/ግለሰቧ ታስረው ሊሆን ይችላል፤ በሌሎች ጉዳዮች ደግሞ በእምነት ቃል ወይም በዋስ ተለቅቀው ሊሆን ይችላል፡፡
  • በማስተር ካሌንደር መሰሚያ ጊዜ ተጠሪ ከጠበቃቸው ጋር ወይም በራሳቸው ቀርበው የክስ መዛግብት ተብለው ለሚጠሩት ሰነዶች ምላሽ ይሰጣሉ፤ ከዚያም ከአገር ማስወጣት እንዳይፈጸምባቸው ለማድረግ እንደ አንድ መከላከያ ጥገኝነት እየጠየቁ መሆኑን ለፍርድ ቤቱ ያሳውቃሉ፡፡ ከዚያም ፍርድ ቤቱ ሰነዶች እና ማስረጃዎች የሚቀርቡበትን ጊዜ ጨምሮ ጉዳዩ የሚሰማበትን ቀነ ቀጠሮ ይሰጣል፡፡
  • ይህ ቃለ መጠይቅ ማንነታቸውን ለማረጋገጥና አሜሪካ ውስጥ ለመኖር የሚያስችል ሕጋዊ ፈቃድ መኖር አለመኖሩን ለማረጋገጥ እንዲሁም ከመጠረዝ /መባረር መከላከያዎች ለመስጠትና ማመልከቻዎችን ለማስገባት፡፡ ከዚህ ባሻገር የማስተር ካሌንደር መሰሚያ በርካታ ተጠሪዎች ከነበርካታ ጉዳዮቻቸው የሚቀርቡበት ነው፤ ሆኖም እያንዳንዱ ጉዳይ በሚሰማበት ጊዜ የሚሰማው/የምትሰማው የጉዳዩ ተጠሪ ብቻ ናቸው፡፡ ተጠሪ የምስክርነት ቃላቸውን ይሰጣሉ፣ ታሪካቸውን የሚደግፉላቸው ሌሎች ምስክሮችን እና ሰነዶችን ያቀርባሉ፡፡ የፍርድ ቤት ሂደቱ የሚጀምረው የተጠሪው ጠበቃ በሚጠይቋቸው ጥያቄዎች ሲሆን ከዚያም ተጠሪ በመንግስት ጠበቃ መስቀለኛ ጥያቄዎችን ይጠየቃሉ፡፡ ሌሎች ምስክሮች ካሉ በተመሳሳይ መልኩ ይቀጥላል፡፡ አስፈላጊ ሲሆን ዳኛው/ዳኛዋ ጣልቃ ገብተው ጥያቄዎችን ሊጠይቁ ይችላሉ፡፡ መስቀለኛ ጥያቄዎች ከቀረቡ በኋላ በመስቀለኛ ጥያቄ ጊዜ አሻሚ ሆነው የቀሩ ወይም ሳይገለጹ የታለፉ ጉዳዮች ካሉ የተጠሪ ጠበቃ ማጣሪያ ጥያቄዎችን ሊጠይቁ ይችላሉ፡፡
  • ጉዳዩ ተሰምቶ ሲጠናቀቅ ዳኛው/ዳኛዋ በዚያው ወይም በሌላ ቀን ውሳኔ ይሰጣሉ፡፡ ውሳኔው ጥገኝነት የመስጠት ወይም ያለመስጠት ይሆናል፡፡ ማመልከቻው ተቀባይነት ካላገኘ ተጠሪ ለኢሚግሬሽን የይግባኝ ቦርድ በሰላሳ ቀናት ውስጥ የይግባኝ አቤቱታ ማቅረብ ይችላሉ፡፡ በአንፃሩ መንግስትም የጥገኝነት ጥያቄው መፈቀዱን ከተቃወመ ይግባኝ ማቅረብ ይቻላል፡፡
  • በተፋጠነ ስርዓት አቤቱታው ውድቅ እንዳይደረግ የይግባኝ ማሳወቂያው የይግባኙን የሕግ እና የፍሬ ነገር መሠረቶች በግልጽ ማስፈር ይኖርበታል፡፡ ከዚያም ይግባኙን የሚደግፍ ተጨማሪ ዝርዝር ጉዳዮችን የያዘ የሕግ አቤቱታ ለማስገባት የኢሚግሬሽን የይግባኝ ቦርድ ‹‹የአጭር መግለጫ›› ቀነ ቀጠሮ (briefing schedule) ይይዛል፡፡
  • ቦርዱ ይግባኙን ሊቀበል፣ ጉዳዩ እንደገና እንዲታይ ወደ ፍርድ ቤቱ ሊመራው ወይም የሥር ጽ/ቤቱን ውሳኔ ሊያጸና ይችላል፡፡ ቦርዱ ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት መልሶ ከመራው ጉዳዩ ቀደም ሲል ወደታየበት ፍርድ ቤት ሄዶ ዳኛው/ዳኛዋ ቀደሞ የተሰጠውን ውሳኔ በቦርዱ ከተሰጡት መምሪያዎች አንጻር እንዲያዩት ይደረጋል፡፡ ቦርዱ ይግባኙን ካልተቀበለው የሚቀጥለው የይግባኝ ሂደት የሚካሄደው ጉዳዩን የማየት ስልጣን ባለው የሰርኪዩት ፍርድ ቤት (Circuit Court) ይሆናል፡፡